ድሮ ከልጆች ጋር ስንጫወት ተመትተን
ከመጣን ወላጆቻችን ይቆጣሉ፡፡ ‹ለምን ታለቃቅሳለህ› የሚለው የመጀመሪያ ቁጣቸው ነው፡፡ ወይ እዚያው ታግለህ አሸንፈህ መምጣት ነው፤
አለያም ደግሞ መሸነፍህን አምነህ በቀጣይ እንዴት እንደምታሸንፍ ማሰብ ነው፡፡ ማለቃቀስ መፍትሔ አይሆንም፡፡
ሦስተኛ ክፍል እያለሁ ሙሉጌታ የሚባል
ልጅ እኛ ክፍል ነበረ(ስሙ ተለውጧል)፡፡ ሙሉጌታ እንደ ጸጋዬ የሚፈራው አልነበረም፡፡ ልጆቹም ተንኮለኞች ናቸው መሳቅ ሲፈልጉ ሙሉጌታና
ጸጋዬን ማጋጠም ይወዳሉ፡፡ ጸጋዬ ወፍራም ነው፡፡ ሙሉጌታን ከመሬት ጋር ይሰፋዋል፡፡ ሙሉጌታ ሦስት ጊዜ ይቀጣል፡፡ ጸጋዬ ያደባየዋል፡፡
ልጆቹ ይስቁበታል፡፡ እናቱ ደግሞ ‹እያለቃቀስክ አትምጣ፣ የአንተ እጅስ ሙቅ ይዟል ወይ!› ብለው ይገርፉታል፡፡
አንድ ቀን የሳይንስ አስተማሪያችን
ስለ ኃይል ሰጭ ምግቦች አስተማረን፡፡ ድንች ኃይል እንደሚሰጥ ከነ ሥዕሉ አሳየን፡፡ የሙሉጌታ ዓይኖች በሩ፡፡ ልቡ ሞቀ፣ አዲስ
ሐሳብ የተገለጠለት መሰለው፡፡ እናቱ የድንች ነጋዴ ናቸው፡፡ ቤቱ የቅዳሜ ገበያ ፊት ለፊት ነበር፡፡
ቤቱ እንደገባ ድስት ሙሉ የድንች
ቅቅል በሚጥሚጣ አስቀርቦ ራቱን በላ፡፡ ጠዋትም ቁርሱ እርሱ ነበር፡፡ ከዳንቴል በተሠራው ቦርሳው አንድ አምስት ድንች ይዞ መምጣቱ
ትዝ ይለኛል፡፡