የፍልስፍናው ይዘታዊ
ማስረጃዎች
ኮንቲ ሮሲኒ እንደሚለው የሐተታ
ዘርአ ያእቆብን ፍልስፍና ከዳ. ኡርቢኖ ደብዳቤዎች ጋር ለማስተያየት ሞክሮ ነበር፡፡ ዳ. ኡርቢኖ በግንቦት 1854 ለአንቶንዮ ዲ.
አባዲ በጻፈው ደብዳቤ ላይ ሰውን የዚህ ዓለም ማዕከል አድርጎ የሚያይበትን አመለካከቱን አንጸባርቆ ነበር፡፡ ይህም አስተሳሰብ በሐተታ
ዘርአ ያእቆብ ላይ በዚያው መልኩ ይገኛል፡፡ ኡርቢኖ ‹አንዳች ነገር ባውቅ ያ ከእግዚአብሔር ያገኘሁት ነው፡፡ ማንም አላስተማረኝም..
ስለ ፈጣሪና ሀልዎቱ እውነት የሆነ ሐሳብ እንዳለኝ አምናለሁ፡፡ ይህንንም ከማንም ባለመቀበሌ እኮራለሁ› ሲል በደብዳቤው ላይ ገልጦታል፡፡
በመስከረም 1854 በጻፈው ሌላ ደብዳቤ ደግሞ ብቸኝነቱ ከፈጣሪና ከዓለማት ጋር ለመገናኘትና በደስታ ለመኖር የሚቻልበትን መንገድ
ለመመርመር እንደገፋፋው ይገልጣል፡፡ ‹እግዚአብሔር መኖሩን አምናለሁ፤ ሌላው ነገር ግን ሊያረካኝ ስላልቻለ እቃወመዋለሁ› ሲል ገልጦ
ነበር፡፡ ይህን መሰሉ ሐሳብ በሐተታ ዘርአ ያእቆብም ውስጥ ይገኛል፡፡ በርግጥ ይህንን ደብዳቤ የጻፈው ሐተታ ዘርአ ያእቆብን ካገኘ
ከሁለት ዓመታት በኋላ በመሆኑ ማን ከማን እንደወሰደው ግልጽ አይደለም የሚል ትችት ቀርቦበታል፡፡ ነገር ግን ቀደም ብሎ ከጻፋቸው
ብቸኝነቱን ከሚጠቅሱት ደብዳቤዎቹ ጋር ስናነጻጽረው ይህ ሐሳብ የ ዳ. ኡርቢኖ ውስጣዊ ሐሳቡ መሆኑን እንረዳለን፡፡