ቅዱስ ሲኖዶስ የፓትርያርኩን እንደራሴ
ሹመት በተመለከተ ለመወያት የያዘው አጀንዳ የመንግሥት ተወካይ ባለበት እንዲታይ መወሰኑን ዛሬ ጠዋት ሰማን፡፡ ከብጹዐን ጳጳሳት
በቀር ካህናትና ቆሞሳት እንኳን የማይገቡበት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አማኝ ይሁን ኢአማኒ፣ ሙስሊም ይሁን ክርስቲያን የማይታወቅ የመንግሥት
ተወካይ እንዲገኝበት መጋበዙ የደረስንበትን የውርደት ደረጃ የሚያሳየን ነው፡፡
በአንድ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ
በቤተ ክርስቲያኒቱ ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ ወሳኝ አካል መሆኑን ስናስበው፤ በሌላ በኩል የቅዱስ
ሲኖዶስ ጉባኤ የሚደረገው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ነው፤ ውሳኔውም በሐዋርያት ሥራ እንደተገለጠው ‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› የሚባልበት
ነው(የሐዋ. 15፣29) የሚለውን ስናየው ‹የመንግሥት ተወካይ ይኑርልን› የሚለውን ውሳኔ ኢሃይማኖታዊ ነው ያሰኘዋል፡፡ ለአንድ
የሲኖዶስ ጉባኤ የመንፈስ ቅዱስ መገኘት አልበቃው ብሎ ነው የመንግሥትን ተወካይ የሚጋብዘው? ‹ሱባኤ ይዘን፣ ጸሎት አድርገን፤ አንድ
ገዳም ወርደን፣ ከእግዚአብሔር ጋር መክረን› አይደለም ይሉን አባቶቻችን፡፡ ‹የመንግሥትን ተወካይ ጋብዘን› ነው ያሉን፡፡ እንዲያውም
ቀኖናው የሊቀ ጳጳሳቱ(ፓትርያርኩ) ጉዳይ ሲታይ ‹በመቀመጫቸው መካከል አንድ ወንበር አስቀምጠው፣ ቅዱስ ወንጌሉን በዚያ ላይ አኑረው፣
ሊቀ ጳጳሳቱ በፊታቸው ተቀምጦ፣ አንድነት ተነሥተው በሩን ዘግተው ይጸልዩ፤ የተሰበሰቡበትንም ጉዳይ በሥውር(በኅቡእ) ይመርምሩ›
ነው የሚለው(ፍ.ነ. ዐ.168)፡፡ እንዴት ተደርጎ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የሚታየው? አግዚአብሔር ያየናል የሚለው ጠፍቶ
ታዛቢ ቢያስፈልግ እንኳን የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ለታዛቢነት አይበቁም? ቅዱስ ጳውሎስ ‹በወንድሞች መካከል ሽማግሌ ሊሆን የሚችል
አንድ አስተዋይ ሰው በእናንተ ዘንድ አይገኝምን?› (1ኛቆሮ. 6፣5) ያለው ለዚህ ጊዜ አይሆነንም?