ኩራዝ ከጓሮ ማድቤት ተወሽቃ
ትኖር ነበር፡፡ ለብዙ ዘመናት፡፡ ድንገት ሳሎን የምግብ ጠረጲዛ ላይ ታየች፡፡ ይህ ነገር ኮርኒስ ላይ የተንጠለጠለችውን አምፖል
በእጅጉ አስገረማት፡፡
‹‹ኩራዝ፣ ዛሬ ከየት ከየት
ተገኘሽ፡፡ እኔኮ እንደ ዳይኖሰር ዝርያሽ የጠፋ መስሎኝ ነበር›› አለች አምፖል እየተወዛወዘች፡፡
‹‹እናንተ የተጋደመ አታስተኙ፣
የተቀበረ አታስሞቱ›› አለቻት ኩራዝ ብል ብል እያለች፡፡ በዙሪያዋ የቤቱ ባለቤቶች ከብበው እራት ይበላሉ፡፡ ከተመጋቢዎቹ አንዱ
ጭል ጭል በምትለው የኩራዟ ብርሃን በእንጀራው መሐል ያለውን ወጥ ፍለጋ ጠጋ ብሎ እያየ እንዲህ አለ፡-
‹‹ዛሬ ፌስ ቡክ ላይ ያየሁትን
ግጥም ልንገራችሁ››
‹‹ምን ተባለ ደግሞ፡፡ ድሮ
እረኛ ምን አለ? ነበር የሚባለው፡፡ ዛሬማ ፌስ ቡክ ምን አለ ሆነኮ፡፡›› አለችው የአባ ወራው ሚስት ወጡን ያገኘው ዘንድ
ኩራዙን እያስጠጋችለት፡፡