Friday, May 24, 2013

ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት (1935-2013) ዐረፉ

click here for pdf


ኢትዮጵያ የመካከለኛው ዘመን ታሪክ ሊቅ የሆኑትና አያሌ መጻሕፍትንና የጥናት ጽሑፎችን በልዩ ልዩ ብሔራዊና ሀገር ዐቀፍ መድረኮች ያቀረቡት፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሚገኘው የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም እንዲመሠረት ተጋድሎ ካደረጉ ምሁራን አንዱ የሆኑት፣ የኢትዮጵያ ጥንታዊ መዛግብት በማይክሮ ፊልም እንዲሰባሰቡ፣ እንዲጠኑና እንዲታወቁ ከደከሙት የመጀመርያዎቹ ሊቃውንት መካከል የሚቆጠሩት፣ ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት ግንቦት 15 ቀን 2005 ዓ.ም. በአሜሪካን አገር ቺካጎ ከተማ ዐረፉ፡፡

Thursday, May 23, 2013

የሃይማኖት ተቋማት ምዝገባ መመሪያ፣ አንዳንድ ነጥቦች



የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ረቂቅ መመሪያ መዘጋጀቱን፣ መመሪያውም ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አንጻር የማያስኬድባቸውን አጠቃላይ ጉዳዮች ባለፈው አንሥተን ነበር፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰሞኑን የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን ሲገመግም በሕግ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኩል ካነሣቸው ነጥቦች አንዱ ወደ ምክር ቤቱ የሚመጡ ሕጎች በሚገባ ረቅቀው፣ ተሰልቀውና የማያዳግሙ ሆነው ከመምጣት ይልቅ በሚገባ ሳይዘጋጁ በመምጣታቸው በጥቂት ጊዜ ውስጥ ማሻሻያ በማውጣት የምክር ቤቱ ጊዜ እየባከነ፣ የሕጎችንም ደረጃ እያስገመተ መሆኑን ነው፡፡ አሁንም ይህ የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ የወጣው መመሪያ ምክር ቤቱ የሰጠውን ተግሣጽ የተከተለ ይሆን ዘንድ ሊታዩ የሚገባቸውን ሃሳቦች አቅርበናል፡፡

Tuesday, May 21, 2013

ይድረስ ለማታውቁን ለምናውቃችሁ



እንዴው በዚያ የደቡብ አፍሪካው የአፍሪካ ዋንጫ ሰሞን እጅግ የታወቁት የእንግሊዝ እግር ኳስ አሠልጣኝ አንዱን እንኳን የብሔራዊ ቡድናችንን ተጫዋች ስም መጥራት አቃታቸው አሉ፡፡ ትዝብት ነው፡፡ እኛ ከነጫማና ከነከናቴራ ቁጥራችሁ ልቅም አድርገን ስናውቃችሁ፤ ምነው ጃል እንዲያ ሠላሳ ዓመት ለፍተን ያፈራናቸውን ተጨዋቾች እንዴት ስማቸውን አያውቋቸውም፡፡
ለመሆኑ ኢትዮጵያን የማያውቅ ሰው የእንግሊዝን እግር ኳስ ማሠልጠኑ ራሱ ተገቢ ነበር? ይህችን በአፍሪካ ውስጥ ቅኝ ያልተገዛች፣ በአድዋ ጦርነት ነጭን ያንበረከከች፣ የራስዋ ፊደልና ዜማ ያላት፣ የራስዋ ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ያላትን፣ በዓለም አንደኛ የሆነችውን ኢትዮጵያን ሳያውቁ እንዴት የእንግሊዝን ትልቅ ክለብ ሊያሠለጥኑ በቁ፡፡ እነዚህ ፈረንጆች ለእግር እንጂ ለጭንቅላት ግድ የላቸውም ማለት ነው? እነዚህን ልጆች ለማፍራት ሠላሳ ዓመት እንደፈጀብን እንዴት አድርገን በነገርንዎ፤ ታድያ እነዚህን ዓለም ያወቃቸውን ልጆቻችንን ካላወቋቸውማ ሌሎቻችንንማ ከነመፈጠራችንም አያውቁንም ማለት ነው፡፡

Friday, May 17, 2013

እውነትን ለመቅበር

እውነት እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ዘለዓለማዊ ነው፡፡ እውነትም ዘለዓለማዊት ናት፡፡ <የሰዎችን ልጆች ጥላዎች> ሲያስበረግጉ ከኖሩት ነገሮች አንዷ እውነት ናት፡፡ ‹የሰዎች ልጆች ጥላዎች› ያልኩት ሰው ከሚለው ስያሜ ለመለየት ነው፡፡ እነዚህ እውነትን የሚፈሯትና የሚጠሏት አካላት ሰዎች አይደሉም፡፡ ሰው እውነትን ይወዳል፣ በእውነትም ይኖራል፣ ለእውነትም ይሞታል፡፡ እርሱ በእውነት እጆች የተፈጠረ ነውና፡፡ ነገር ግን <የሰው ጥላዎች> አሉ፡፡ ሰዎች ያልሆኑ፤ ነገር ግን የሰው መልክ ያላቸው፣ ራስ ያላቸው ነገር ግን አእምሮ የሌላቸው፣ ሆድ ያላቸው፣ ነገር ግን ልቡና የሌላቸው፣ አፍ ያላቸው ነገር ግን አንደበት የሌላቸው፣ ጉሮሮ ያላቸው ነገር ግን አንገት የሌላቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች አይደሉም፡፡ እነዚህ ‹የሰው ጥላዎች› ናቸው፡፡ ጥላ እንደሚጠፋው እነርሱም ይጠፋሉ፤ ጥላን ብርሃን እንደሚያጠፋው እነርሱንም የእውነት ብርሃን ያጠፋቸዋል፡፡
በሰሞነ ሕማማት የተፈጸመው ድርጊት ይኼው ነበር፡፡ የሰው ጥላዎች እውነትን ለመግደል ያደረጉት ሙከራ፡፡ እነዚህ የሰው ጥላዎች ራሳቸውን እውነተኛ ከማድረግ ይልቅ አውነትን በመግደል ሐሰተኛነታቸውን መሸፈንና እንደማንነታቸው ሁሉ በእውነት ጥላ መኖር ነበር የፈለጉት፡፡ ክርስቶስ እውነት ነው፤ ያስተማረውም እውነት ነው፤ ለሐሰት አንድም ቦታ ሳይሰጥ የገለጠው እውነትን ነው፡፡ ይህ እውነት ግን መኖሪያቸውንና ማንነታቸውን ሐሰት ላደረጉት ‹የሰው ጥላዎች› አልተመቻቸውም፤ አመማቸው፤ በየጊዜው ራሳቸውን እንዲያዩና ራሳቸውን እንዲወቅሱ ስላደረጋቸው አመማቸው፤ የእውነት መኖር ሐሰትን ማንጸርያ ስለሚያመጣባት አመማቸው፤ ብቻቸውን ሆነው ያለምንም ማንጸሪያ ነን ያሉትን ሁሉ እየታመኑ እንዲኖሩ ነበር ሃሳባቸው፤ ነገር ግን እውነት መጣችና ከጎናቸው ስትቆም በቀላሉ ጥላው ከብርሃኑ ተለየ፡፡ ብርሃን ከሌለ ጨለማን፣ ቀን ከሌለ ሌሊትን፣ ሕይወት ከሌለ ሞትን፣ ክብር ከሌለ ውርደትን፣ ነጻነት ከሌለ ባርነትን በምን መለየት ይቻላል፡፡

Tuesday, April 30, 2013

ከ2000 ዓመት በኋላ እንደ አዲስ እንመዘገባለን፣ እንደ አዲስም እንታወቃለን


ሰሞኑን የፌድራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ የወጣ ረቂቅ መመሪያ› የሚል ወረቀት አስተያየት ይሰጥበት ዘንድ ለእምነት ተቋማት አሠራጭቷል፡፡ ይህ መመርያ የያዛቸውን ጉዳዮች እያንዳንዳቸውን እየነጠሉ መመልከት ያስፈልጋል፡፡ ይህንንም ወደፊት የምናደርገው ይሆናል፡፡ ለአሁኑ ግን መመሪያውን ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ነባራዊ፣ ሉዓላዊና መንፈሳዊ ጠባያት ጋር በማዛመድ ብቻ እንመለከተዋለን፡፡
1.       መመሪያው የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዩ ሁኔታ ከግምት ያላስገባ ነው
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላለፉት 2000 ዓመታት በምድሪቱ ላይ የኖረች፣ የሰበከች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በሀገሪቱ ታሪክ ውስጥ ክፉውንም ሆነ ደጉንም እኩል የቀመሰች፣ እንዲያውም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በመሆንዋ ብቻ ልዩ ጉዳት የደረሰባትም ናት፡፡ በጣልያን ወረራ ጊዜ የተሠውትን ጳጳሳትና መነኮሳት ማሰቡ ብቻ ለዚህ የቅርብ ምሳሌ ነው፡፡ ይህቺ ቤተ ክርስቲያን በዘመናት ሂደት ውስጥ በሀገሪቱ ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሕይወት ውስጥ ልዩ የሆነና የማይተካ ሚና ተጫውታለች፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ተመሥርታ ሀገሪቱንም መሥርታለች፡፡
ይህንን ሁሉ ዘንግቶ በ2005 ዓም ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱን እንደ አዲስ ተመዝገቢ፣ እንደ አዲስ ፈቃድ አውጭ፣ እንደ አዲስ ደንብና መመሪያሽን አምጭ ማለት እጅግ አሳዛኝም አስገራሚም ነገር ነው፡፡ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱም ራሱ ከፈለገ መረጃ ሰብስቦ መመዝገብና ማወቅ ነበረበት እንጂ ሰነድ አምጭ፣ ደንብ አስገቢ፣ ፈቃድ አውጭና ልወቅሽ ማለት አልነበረበትም፡፡

Tuesday, April 23, 2013

አማርኛ ከሠላሳ ዓመት በኋላ



 
የዛሬ ሠላሳ ዓመት በ2035 ዓም በአዲስ አበባ ትምህርት ቤቶች መካከል የአማርኛ ሥነ ጽሑፍ ውድድር ይደረጋል፡፡ በውድድሩም ከዚህ በታች የማቀርብላችሁ ወግ ‹እኔና ትምህርት ቤቴ› በሚል ርእስ ተወዳድሮ አንደኛ ይወጣል፡፡
ይህ ኦፖርቹኒቲ ስለ ተሰጠኝ ታንክዩ፡፡ አቦ ይመቻችሁ፡፡ ሀገራችን ኢቶጲያ ሚራክልየስ ሀገር ናት፡፡ አይ ሚን ነፍስ ነገር ናት፡፡ ይህንን ስል ግን ሙድ እንዳትይዙብኝ፡፡ እዚህ ሀገር ብዙ ነገር ነፍ ነው ማለቴ ነው፡፡ ዋተር ነፍ ነው፣ ኦፕን ኤይር ነፍ ነው፣ ሰን ሴትና ሰን ራይዝ ነፍ ነው፡፡ ማዩንቴይን ነፍ ነው፤ የሚደብረው ነገር ሮዶቹና ቪሌጆቹ ምልክት የላቸውም፡፡ ፎር ኤግዛምፕል የኛን ቤት ለሰው ስንነግር ‹ኒር እንትና ጫት ቤት› ነው የምንለው፡፡ ቢኮዝ እዚህ ሀገር ጫት ቤት ነፍ ነዋ፡፡ አት ዚስ ፖይንት ኤክስፕሌይን ማድረግ አለብኝ፡፡ የአያቴን ካፕ ቦርድ ስሾፍ አዲስ ዘመን የሚባል አንድ የድሮ ኒውስ ፔፐር አገኘሁና፡፡ ኮለመኑ ላይ ‹በምግብ ራስን መቻል› የሚል ነገር ሾፍኩ፡፡ ነገሩ ክሊር አልሆነልኝም ነበር፡፡ ዋት ኢዝ ‹ራስን መቻል›? ራስ ማለት ‹ሄድ› አይለደም እንዴ? መቻልስ ምንድን ነው? አንዱን ፍሬንዴን አስክ ሳደርገው ‹መቻል የሚባል ኦልድ ውሻ ጎረቤታችን አለ› አለኝ፡፡ ስለዚህ ራስን መቻል ሚን ‹የመቻል ራስ› ማለት ነው፡፡ 

Tuesday, April 16, 2013

የዓመቱ ‹በጎ ሰው›

የዳንኤል ዕይታዎች ‹የዓመቱ በጎ ሰው› የምርጫ ኮሚቴ ሰባት አባላት ነበሩት፡፡ እነዚህ አባላት ከተለያዩ ሞያዎችና አካባቢዎች የመጡ ሲሆን በ‹የዳንኤል ዕይታዎች› አማካኝነት ለአንድ ወር ያህል አንባብያን ‹በጎ ሰው› የሚሉትን እንዲጠቁሙ ዕድል ተሰጥቶ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት በ159 ጠቋሚዎች 70 ግለሰቦችና ሰባት ተቋማት ተጠቁመዋል፡፡
እነዚህን 70 ኢትዮጵያውያንና ሰባት ተቋማትን አመዛዝነው አሥር ምርጦችን እንዲሰይሙ በተለያዩ ክልሎችና ሞያዎች ለሚገኙ እርስ በርሳቸውም ለማይተዋወቁ 9 ሰዎች ተሰጠ፡፡ በዚህም መሠረት ከጠቋሚዎችና ከመራጮች የተሻሉ ድምፆችን ያገኙ አሥራ ሰባት ሰዎች ተመረጡ፡፡
እነርሱም